የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ የጋርዱላ ዞን ቴክኒክና ሙያ ትምህርት ሥልጠና ኮሌጅ ግንባታ ቀሪ ሥራዎችን ለማጠናቀቅ ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ጋር የፊርማ ስነ-ስርዓትና የሥራ ዉል ርክክብ ስነ-ስርዓት አካሂዷል ።
በርክክብ ስነስርዓት ላይ ተገኝተዉ ንግግር ያደረጉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብሔረሰቦች ምክር ቤት አፈጉባኤ ክቡር አቶ አዳማ ትንጳዬ የጋርዱላ ዞን ቴክኒክና ሙያ ትምህርት ሥልጠና ኮሌጅ ግንባታ ተጀምሮ በመሃል ረዘም ላለ ዓመታት ከቆመበት ጊዜ አንስቶ የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ግንባታዉን በአዲስ መልክ ለማስቀጠል በልዩ ትኩረት ሲከታተል ቆይቶ ዛሬ ለሰጠዉ ፈጣን ምላሽ አመስግነዋል።
በዞኑ ተጀምሮ ያላለቁ ፕሮጀክቶች የክልሉ መንግስት በሰጠዉ ልዩ ትኩረት አብዛኛዎቹ ተጠናቀዉ አገልግሎት መስጠት መጀመራቸዉን የገለጹት ዋና አፈጉባኤዉ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኮሌጅም የዚሁ አካል ሲሆን የግንባታ ዉል ገብቶ በአዲስ መልክ ሥራዉ ከቆመበት ለማስቀጠል የሚረከበዉ የክልሉ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ግንባታዉን በተቀመጠለት በአንድ ዓመት ጊዜ ዉስጥ እንዲያጠናቅቅ አደራ ብለዋል።
የኮሌጁ ስራ ሲጠናቀቅ የመማር ማስተማሩን ተግባር ምቹና ቀልጣፋ እንደሚያደርገዉ የተናገሩት ዋና አፈጉባኤዉ ለአፈጻጸሙ በየደረጃዉ ያሉ የክልል፣የዞን እና የከተማ አስተዳደር የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች በአስፈላጊዉ ሁሉ የበኩላቸዉን ድርሻ እንዲወጡ አሳስበዋል።
በለዉጡ መንግስት ህዝቡ ለዉጥ ይፈልጋል ያሉት የሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊና የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ሥልጠና ዘርፍ ኃላፊ ኢንጅነር በዛብህ ገበየሁ በበኩላቸዉ ከለዉጡ በኋላ ተጀምሮ ያላለቁና በመንገድ የቀሩ ፕሮጀክቶች በሕዝብ ዘንድ የመልካም አስተዳደር ችግር አጀንዳ ከመሆኑም ባሻገር በመንግስት ላይ ታዓማኒነት የሚቀንስ በመሆኑ የዞኑን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በፍጥነት ለመመለስ የክልሉ መንግስት ከሚመለከታቸዉ ተቋማት ጋር በቅንጅት እየሰራ ነዉ ብለዋል።
የግንባታው ሥራ በ175 ሚሊዮን ብር በአንድ አመት ዉስጥ ለማጠናቀቅ ዉል የተገባ መሆኑን የጠቆሙት የቢሮ ምክትል ሀላፊና የዘርፉ ሀላፊ የግንባታዉ ሥራ እስከሚጠናቀቅ ድረስ የክልሉ ቢሮ ከዞንና ከተማ አስተዳደር ጋር ያለዉ ቅንጅት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን ምክትል ኃላፊና የምህንድስናና ኮንትራት ዘርፍ ሀላፊ ኢንጂነር ኢያሱ እንግዳ በበኩላቸው የተሰጠን ከባድ አደራ መሆኑን ተገንዝበን የግንባታውን ሥራ በተያዘለት ጊዜ አጠናቀን ለማስረከብ ቃል እንገባለን ብለዋል ።
የጋርዱላ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግንኙነት ኪታሞ በበኩላቸው በተለያዩ ምክንያቶች ሥራው በተያዘለት ጊዜ ያለመጠናቀቁን በመግለፅ ሥራዉ ከቆመበት ለማስቀጠል የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ለወሰደዉ እርምጃ በዞኑ ስም አመስግነዉ የዞኑ መንግስት በቀጣይ በግንባታዉ አፈጻጸም ሂደት በሚያስፈልጉ ጉዳዮች ላይ ከኮንትራክተሮቹ ጎን በመቆም ለዉጤት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
ዘገባዉ የሥራና ክህሎት ቢሮ ሕዝብ ግንኙነትና ሚዲያ ኮሚኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ነዉ።

